Amos 7

አንበጣ፣ እሳትና ቱንቢ

1ጌታ እግዚአብሔር ይህን አሳየኝ፤ የንጉሡ የመኸር እህል ከተሰበሰበ በኋላ ገቦው መብቀል በጀመረ ጊዜ፣ እርሱ የአንበጣ መንጋ እንዲፈለፈል አደረገ። 2አንበጦች የምድሩን ሣር ግጠው ከጨረሱት በኋላ፣ “ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ ይቅር እንድትል እለምንሃለሁ፤ ያዕቆብ ይህን እንዴት ሊቋቋመው ይችላል? ታናሽ ነው እኮ!” አልሁ።

3 እግዚአብሔርም ስለዚህ ነገር ተጸጸተ፤ እግዚአብሔርም ይህ አይፈጸምም አለ።

4ጌታ እግዚአብሔር ይህንም አሳየኝ፤ ጌታ እግዚአብሔር በእሳት ሊፈርድ ተዘጋጀ፤ እሳቱም ታላቁን ጥልቅ አደረቀ፤ ምድሪቱንም በላ። 5ከዚያም በኋላ፣ “ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ እንድትተወው እለምንሃለሁ፤ ያዕቆብ ይህን እንዴት ሊቋቋመው ይችላል? ታናሽ ነው እኮ!” አልሁ።

6 እግዚአብሔር ስለዚህ ነገር ተጸጸተ፤ ጌታ እግዚአብሔር፣ “ይህም ደግሞ አይፈጸምም” አለ።

7ይህንም ደግሞ አሳየኝ፤ ጌታ በእጁ ቱንቢ ይዞ በቱንቢ በተሠራ ቅጥር አጠገብ ቆሞ ነበር። 8እግዚአብሔር፣ “አሞጽ፣ የምታየው ምንድን ነው?” አለኝ።

እኔም፣ “ቱንቢ” አልሁ።

ጌታም እንዲህ አለ፤ “እነሆ፤ በሕዝቤ በእስራኤል መካከል ቱንቢ እዘረጋለሁ፤ ከእንግዲህም ወዲያ አልምራቸውም።

9“የይስሐቅ ማምለኪያ ኰረብታዎች ባድማ ይሆናሉ፤
የእስራኤል መቅደሶች ይፈርሳሉ፤
በኢዮርብዓምም ቤት ላይ በሰይፌ እነሣለሁ።”

አሞጽና አሜስያስ

10ከዚህ በኋላ የቤቴል ካህን አሜስያስ ወደ እስራኤል ንጉሥ ወደ ኢዮርብዓም እንዲህ ሲል መልእክት ላከ፤ “አሞጽ በእስራኤል ቤት መካከል በአንተ ላይ እያሤረ ነው፤ ምድሪቱም ቃሉን ሁሉ ልትሸከም አትችልም፤ 11አሞጽ እንዲህ ሲል ተናግሮ ነበርና፤

“ ‘ኢዮርብዓም በሰይፍ ይሞታል፤
እስራኤልም በርግጥ ከትውልድ አገሩ
ተማርኮ ይሄዳል።’ ”
12አሜስያስም፣ አሞጽን እንዲህ አለው፤ “አንተ ባለ ራእይ ከዚህ ሂድ! ከይሁዳ ምድር ሽሽ፤ እዚያም እንጀራህን ብላ፤ በዚያም ትንቢት ተናገር። 13ከእንግዲህ ወዲያ ግን በቤቴል ትንቢት አትናገር፤ የንጉሡ መቅደስ፣ የመንግሥቱም መኖሪያ ነውና።”

14አሞጽም ለአሜስያስ እንዲህ ሲል መለሰ፤ “እኔ እረኛና የባሉጥ ፍሬ ለቃሚ ነኝ እንጂ ነቢይ ወይም የነቢይ ልጅ አይደለሁም፤ 15እግዚአብሔር ግን የበግ መንጋ ከምጠብቅበት ቦታ ወስዶ፣ ‘ሂድና ለሕዝቤ ለእስራኤል ትንቢት ተናገር’ አለኝ፤ 16እንግዲህ የእግዚአብሔርን ቃል ስማ።

“አንተ፣ ‘በእስራኤል ላይ ትንቢት አትናገር፤
በይስሐቅም ቤት ላይ አትስበክ’
ትላለህ።

17“ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

“ ‘ሚስትህ በከተማዪቱ ውስጥ ጋለሞታ ትሆናለች፤
ወንዶችና ሴቶች ልጆችህም በሰይፍ ይወድቃሉ፤
ምድርህም እየተለካ ይከፋፈላል፤
አንተ ራስህ በረከሰ
ዕብራይስጡ ርኩስ ይለዋል።
ምድር ትሞታለህ፤
እስራኤልም ከትውልድ አገሩ፣
ተማርኮ ይሄዳል።’ ”
Copyright information for AmhNASV