Psalms 130

ለርዳታ የቀረበ ጥሪ

መዝሙረ መዓርግ።

1 እግዚአብሔር ሆይ፤ ከጥልቅ ወደ አንተ እጮኻለሁ።
2ጌታ ሆይ፤ ድምፄን ስማ፤
ጆሮዎችህ የልመናዬን ቃል፣
የሚያዳምጡ ይሁኑ።

3 እግዚአብሔር ሆይ፤ ኀጢአትን ብትቈጣጠር፣
ጌታ ሆይ፤ ማን ሊቆም ይችላል?
4ነገር ግን በአንተ ዘንድ ይቅርታ አለ፤
ስለዚህም ልትፈራ ይገባሃል።

5 እግዚአብሔርን ደጅ እጠናለሁ፤ ነፍሴም በትዕግሥት ትጠብቀዋለች፤
በቃሉም ተስፋ አደርጋለሁ።
6ዘብ ዐዳሪ ንጋትን ከሚጠባበቅ ይልቅ፣
አዎን፤ ዘብ ዐዳሪ ንጋትን ከሚጠባበቅ ይልቅ፣
ነፍሴ ጌታን ትጠባበቃለች።

7 በእግዚአብሔር ዘንድ ምሕረት፣
በእርሱም ዘንድ ማዳን አለና፣
እስራኤል ሆይ፤ በእግዚአብሔር ተስፋ አድርግ።
8እርሱም እስራኤልን፣
ከኀጢአቱ ሁሉ ያድነዋል።
Copyright information for AmhNASV